ለሁለት ቀናት በተካሄደው የውይይት መድረክ ላይ የ2017 በጀት ዓመት አፈፃፀም በድርጅቱ የስትራቴጂክ ምሰሶዎች ላይ ተመስርቶ የቀረበ ሪፖርት እና የቀጣይ በጀት አመት እቅዶች በስፋት የተቃኙበት ነበር። ከዚሁ ጋር ተያይዞ የ2017 በጀት ዓመት የላቀ አፈፃፀም የተመዘገበበት እንደሆነ የተነሳ ሲሆን እንደተቋም በቀጣይ ትኩረት ሊሰጥባቸው ይገባል ተብለው በዝርዝር የቀረቡ ጉዳዮች ላይም ውይይት ተደርጓል፡፡
በቀርቡት ሪፖርቶች መሰረት ሊስተካከሉ እና ሊጠናከሩ ይገባቸዋል የተባሉ የስራ ማዕቀፎች ላይ ያተኮሩ ገለጻዎች የተካተቱ ሲሆን እርምት ይፈልጋሉ በተባሉ ነጥቦች ላይም ሰፊ ውይይት ተካሂዶባቸዋል። በቀጣይም የ2018 በጀት ዓመት ሊሰሩባቸው በታሰቡ እቅዶች ላይ ጥልቅ ማብራሪያ ተሰጥቷል።
በመድረኩ ላይ በ2017 በጀት ዓመት የላቀ አፈፃፀም ላስመዘገቡ ዲስትሪክቶች የዋንጫ፣ የሜዳሊያ እና የምስክር ወረቀት ሽልማት ተበርክቶላቸዋል። በውይይቱ መጠናቀቂያ ላይም የኢትዮጵያ ፖስታ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ዳግማዊ ኃይልዬ እንደ ተቋም ለተቀመጠው የ2018 በጀት ዓመት እቅድ በአዲስ ጉልበት እና መነሳሳት ራዕያችንን በትጋት ማስቀጠል ያስፈልጋል ብለዋል። የኢትዮጵያ ፖስታ ከታለመለት ከፍታ ላይ ለማድረስ ከሁሉም የድርጅቱ ሰራተኞች ትጋት እና አገልጋይነት የሚጠበቅ መሆኑን ገልፀዋል።