የኢትዮጵያ ፖስታ ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ዳግማዊ ኃይልዬ ከኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ጋር ባደረጉት ቆይታ ለውጡን ተከትሎ በተሰሩ ተከታታይ የሪፎርም ሥራዎች የኢትዮጵያ ፖስታ ከነበሩበት ችግሮች ተላቆ በብዙ የስራ ትጋትና ጥረት በአንዳንድ አገልግሎቶች በዓለም አቀፍ ደረጃ ለመወዳደር የሚያችል አቅም እንደገነባ ገልፀዋል።
የኢትዮጵያ ፖስታ ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ዳግማዊ ኃይልዬ አክለውም እዚህ ስኬት ላይ የተደረሰው በዋነኝነት የደንበኞች ፍላጎትና የፖስታ አገልግሎት ላይ ጥልቅ ጥናቶችን በማድረግ ሲሆን ይህንንም ተከትሎ የሀገር ውሰጥ እና ዓለም አቀፍ መዳረሻዎችን በማስፋፋት ፣በተመጣጣኝ ዋጋ ጥራት ያለው አገልግሎት በመስጠት እንዲሁም የአገልግሎት መስጫዎችን ምቹ የማድረግ ሥራዎችን በመስራት እንደሆነ ተናግረዋል።
በተጨማሪም አቶ ዳግማዊ ኃይልዬ የኢትዮጵያ ፖስታ በዚህ ሁለንተናዊ ለውጥ በመንግስትም ሆነ በአለም አቀፉ ፖስታ ህብረት ተሸላሚ መሆን እንደቻለ፤ ጥረቶቹንም አጠናክሮ በመቀጠል እና ቀሪ ክፍተቶችን በመሙላት ለተሻለ ስኬት እየተንደረደረ ያለ ልማታዊ የመንግስት ተቋም እንደሆነም ገልፀዋል።





