የኢትዮጵያ ፖስታ የተባበሩት መንግሥታት 80ኛ ዓመት የምሥረታ በዓል ምክንያት በማድረግ ልዩ የመታሰቢያ ቴምብሮች በኢ.ፌ.ዲ.ሪ ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ክቡር ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ አማካኝነት አስመርቋል።
ኢትዮጵያ ከተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ጋር ያላትን የስምንት አስርት ዓመታት የጠበቀ የታሪክ ትስስር፣ የአሁኑን ተሻጋሪ ትብብር እና “በሰላም አብሮ ለመኖር” የተሰነቀውን ዓለም አቀፋዊ እሴት የሚዘክር ልዩ የመታሰቢያ ቴምብር ስብስብ በታላቅ ኩራት አውጥቷል። እነዚህ አራት ቴምብሮች እ.ኤ.አ. በ1945 በሳን ፍራንሲስኮ የተባበሩት መንግሥታት ቻርተርን ከመፈረም ጀምሮ፣ በኮንጎ የሰላም አስከባሪ ኃይሎችን እስከማሰማራት እና በአፍሪካ ምድር ለመጀመሪያ ጊዜ የተካሄደውን የተባበሩት መንግሥታት የጸጥታው ምክር ቤት ስብሰባ እስከ ማስተናገድ ያለውን የጋራ ታሪካችንን በሥነ-ጥበብ የሚተርኩ ናቸው። በዓለም የፖስታ ህብረት በኩል ለ192 ሀገራት የተሰራጩት እነዚህ ቴምብሮች፣ ለኢትዮጵያ ፖስታ ለአንድ ወቅት ብቻ የሚታተሙ ሳይሆኑ ለትውልድ ሁሉ የሚተርፍ የታሪክ ዐሻራ እና የኢትዮጵያ የዲፕሎማሲ ልዕልና ማሳያ ሆነው ይቆያሉ።
የኢትዮጵያ ፖስታ የሀገራችንን ብሔራዊ ጥቅም ለማስጠበቅና ታሪካዊ እሴቶቻችንን በዓለም አቀፍ መድረክ ለማስተዋወቅ በቁርጠኝነት እየሰራ ይገኛል። ይህንን ታላቅ ኩነት አስመልክቶ የወጣው ልዩ የመታሰቢያ ቴምብርም ተቋማችን የኢትዮጵያን የዲፕሎማሲ ስኬት ለዓለም በማብሰር ረገድ ያለውን ሚና የሚያጎላ ነው። በዚህ ታሪካዊና ኩራት በተሞላበት አጋጣሚ ውስጥ ተሳታፊ በመሆናችን ታላቅ ክብር ይሰማናል።





