የኢትዮጵያ ፖስታ እና የኢትዮ ላይፍ ኤንድ ጄኔራል ኢንሹራንስ ኩባንያ “ልባም” የተሰኘውን የዲጂታል የህይወት መድን መተግበሪያ በመላው ሀገሪቱ ተደራሽ ለማድረግ የሚያስችል የትብብር ስምምነት ተፈራርመዋል። ስምምነቱን የኢትዮጵያ ፖስታ ቺፍ ኮሜርሻል ኦፊሰር ወ/ሮ ትዕግስት በቀለ እና የኢትዮ ላይፍ ኤንድ ጄኔራል ኢንሹራንስ ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ሽመልስ ገድለ ጊዮርጊስ የፈረሙት ሲሆን፣ ዋና ዓላማውም የኢትዮጰያ ፖስታን ሰፊ ተደራሽነት በመጠቀም ህብረተሰቡ የዲጂታል የህይወት መድን አገልግሎት ተጠቃሚ እንዲሆን ማስቻል ነው።
ወ/ሮ ትዕግስት የህይወት መድን ለዜጎች ያለውን ዘላቂ ዋስትና ጠቅሰው ተቋሙ የኢትዮጵያ ፖስታን ተደራሽነት ለመጠቀም መወሰኑ የሚደነቅ መሆኑን ሲገልጹ፣ አቶ ሽመልስ በበኩላቸው ከአንጋፋው ተቋም ጋር መስራት ለኢንሹራንስ ዘርፉ ዕድገት ትልቅ መሰረት እንደሚጥል አመልክተዋል። የኢትዮጵያ ፖስታ ከባንኮችና ከቴሌኮም ኩባንያዎች ጋር በዲጂታል ፋይናንስ ሲሰራ የቆየ ቢሆንም፣ የዲጂታል የህይወት መድን አገልግሎት መስጠት የሚጀምርበት ይህ ስምምነት ለመጀመሪያ ጊዜ የተደረገ መሆኑ ተገልጿል።













