የኢትዮጵያ ፖስታ ማህበራዊ ኃላፊነቱን የመወጣት አንድ አካል አድርጎ በተለያዩ ዙሮች ለመቄዶኒያ የአረጋውያን እና የአእምሮ ህሙማን መርጃ ማዕከል የተለያዩ ድጋፎችን ማድረጉ ይታወሳል፡፡
ዛሬም ይህን መልካም ተግባሩን በማስቀጠል፣ ግምታቸው 1,424,500.00 (አንድ ሚሊዮን አራት መቶ ሃያ አራት ሺህ አምስት መቶ) ብር የሆኑ ልዩ ልዩ ድጋፎችን ለመቄዶኒያ የአረጋውያን እና የአእምሮ ህሙማን መርጃ ማዕከል አስረክቧል።
ለተቋሙ የተደረገው ይህ ሰብአዊ ድጋፍ ልዩ ልዩ አልባሳትን፣ የሃይማኖት መጻሕፍትን እና ሌሎች ለተረጂዎች አስፈላጊ የሆኑ ቁሶችን ያካተተ መሆኑ ተገልጿል።
በርክክብ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ የኢትዮጵያ ፖስታ የሰው ሀብት አስተዳደር ቺፍ ኦፊሰር አቶ ተሾመ ቢረዳ እንደገለጹት፤ ተቋሙ ማህበራዊ ግዴታውን ለመወጣት ከፍተኛ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ይገኛል ብለዋል። አቶ ተሾመ አክለውም፣ ድርጅቱ ከገንዘብ እርዳታ ባለፈ በቁሳቁስ ጭምር የሚያደርገው ድጋፍ በቀጣይነት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።
በመጨረሻም በዕለቱ የድጋፍ ርክክቡ በሚከናወንበት ወቅት በማዕከሉ በሚረዱ አባቶችና እናቶች የምርቃት ሥነ-ሥርዓት ተካሂዷል።














