የኢትዮጵያ ፖስታ ከኢት-ስዊች አክሲዮን ማሕበር ጋር አብሮ ለመስራት የሚያስችለውን ስምምነት ተፈራረመ።
በስምምነት ፊርማ ስነስርዓቱ ላይ የኢትዮጵያ ፖስታ እና ኢትስዊች አክሲዮን ማሕበር የተፈራረሙት ስምምነት የኤጀንት ኔትወርክ ማኔጅመንት መተግበሪያን በጋራ ለማበልፀግ ያለመ እንደሆነ ተነግሯል።
የኢትዮጵያ ፖስታ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ዳግማዊ ኃይልዬ የተደረሰው ስምምነት እንደተቋም በኢትዮጵያ ፖስታ የሶስት ዓመት ስትራቴጂክ ፕላን ላይ ትልቅ እመርታን የሚያመጣ መሆኑን ገልፀው በቅርቡ ወደ ትግበራ እንደሚገባ ያላቸውን እምነት ገልፀዋል። በዝግጂቱ ላይ የኢትስዊች አክሲዮን ማሕበር ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ይለበስ አዲስም በበኩላቸው ተቋማቸው ከኢትዮጵያ ፖስታ ጋር ይሕን ስምምነት በማድረጉ የተሰማቸውን ደስታ ገልፀው የኦን ላይን ግብይት አከፋፈል ስርአቱን እና የውክልና ባንኪንግ ስራን (agency banking ) በእጅጉ ሊያግዝ የሚችል እንደሚሆን ገልፀዋል።
በተያያዘም ይህን ስምምነት ከታለመለት ግብ ለማድረስ የማስፈጸሚያ ሰነድ ( functional specification document ) በኢትዮጵያ ፖስታ ቺፍ ኮመርሺያል ኦፊሰር ወ/ሮ ትዕግስት በቀለ እና በኢትስዊች ቺፍ ፖርቲፎሊኦ ኦፊሰር አቶ አቤኔዘር ላቀው በኩል ተፈርሟል። መጨረሻም በሁለቱም ተቋማት በኩል ለዚህ ስምምነት መሳካት ጥረት ያደረጉ አካላት ምስጋና ተችሯቸዋል።














