በአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ ከመላው ሀገሪቱ የተውጣጡ የድርጅቱ አመራሮች በተሳተፉበት እና ለተከታታይ አራት ቀናት ሲካሄድ በቆየው መድረክ ላይ እንደተገለጸው፤ ተቋሙ በ2018 በጀት ዓመት 3.85 ቢሊዮን ብር ገቢ ሰብስቧል። ይህ አፈጻጸም ከባለፈው በጀት ዓመት ጋር ሲነጻጸር የ30 በመቶ ዕድገት ያሳየ ሲሆን፣ ተቋሙ በሌሎች ቁልፍ የአፈጻጸም መለኪያዎችም አመርቂ ውጤት ያስመዘገበበት ስኬታማ ዓመት ሆኖ አልፏል።
በተጨማሪም የቀደመውን “በጥልቀት እና በስፋት” የተሰኘውን የስትራቴጂ እቅድ በተሳካ ሁኔታ ያጠናቀቀ ሲሆን፣ አዲስ የሶስት ዓመታት ስትራቴጂ በመቅረፅ ቴክኖሎጂ-መር እና ደንበኛ-ተኮር አገልግሎቶችን ለማቅረብ ከምንጊዜውም በላይ በላቀ መነሳሳት ወደ ተግባር ለመለወጥ ጠንካራ አቋም ተይዟል።
በመዝጊያ ስነ-ስርዓቱ ላይ በ2018 በጀት ዓመት የላቀ አፈጻጸም ላስመዘገቡት የጂ.ፒ.ኦ (GPO)፣ የአዲስ አበባ እና ምስራቅ ዲስትሪክቶች የዋንጫ እና የእውቅና ሰርተፊኬት ሽልማት ተበርክቶላቸዋል።
የኢትዮጵያ ፖስታ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ዳግማዊ ኃይልዬ በመዝጊያ ንግግራቸው፥ አዲሱን የስትራቴጂክ ፕላን ወደ ሙሉ ተግባር ለመቀየር እና የ2019 በጀት ዓመት እቅዶችን ስኬታማ ለማድረግ የጠንካራ አመራር እና የሰራተኞች የተቀናጀ ርብርብ ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። ዋና ሥራ አስፈፃሚው አክለውም እያንዳንዱ አመራርና ሰራተኛ የተጣለበትን ሀላፊነት በመወጣት ተቋሙ የጀመረውን የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ጉዞ ዳር ለማድረስ የበኩሉን አስተዋጽኦ እንዲያበረክት ጥሪ አቅርበዋል።










