የኢትዮጵያ ፖስታ ከኦሮሚያ ጤና ቢሮ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች ጋር በመገናኘት በክልሉ የሚገኙ የጤና ናሙና ሎጂስቲክስ፣ የፋይናንሺያል እና የመልዕክት አገልግሎቶችን በቅንጅት መስጠት ላይ ያተኮረ የትብብር ስራዎችን ለመስራት የሚያስችል ውይይት አካሂዷል። የኢትዮጵያ ፖስታ ላለፉት አስር አመታት ከኢትዮጵያ ህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር በመላ ሀገሪቱ ከሚገኙ የመንግስት የጤና ተቋማት የጤና ናሙናዎችን ተቀብሎ ወደ መመርመሪያ ጣቢያዎች በማድረስና ውጤቱንም መልሶ ለጤና ተቋማት በማስረከብ የሎጅስቲክስ አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል። ይህ አሰራር በናሙና ዝውውር ላይ የሚስተዋሉ ተግዳሮቶችን በመፍታት ለህብረተሰቡ የጤና ሽፋንን ከመጨመር አንፃር ከፍተኛ አስተዋፅኦ አድርጓል።
በኦሮሚያ ጤና ቢሮ ስር ከሚገኙ የዞንና ከተማ ጤና ቢሮ ኃላፊዎች ጋር የተደረገው ይህ ውይይት የጤና ናሙና ሎጂስቲክስን በቴክኖሎጂ ማዘመንና አጋርነትን ከፍ በማድረግ ለህብረተሰቡ ይበልጥ ተደራሽ መሆን ላይ ያተኮረ ነበር። ይህንንም ለመተግበር የኢትዮጵያ ፖስታ በኦሮሚያ ጤና ቢሮ ሥር በሚገኙ 1440 የጤና ተቋማት ውስጥ የአገልግሎት መስጫ ቦታዎችን ለማግኘት የሚያስችል ስምምነት ላይ ተደርሷል። በሚቀጥሉት ጥቂት ወራት ውስጥ የኢትዮጵያ ፖስታ የናሙና አሰባሰብ ሂደቱን ለማቀላጠፍ እና ለአካባቢው ማህበረሰብ ተጨማሪ አገልግሎቶችን ለመስጠት ከኦሮሚያ ጤና ቢሮ ጋር በመተባበር በነዚህ የጤና ተቋማት ውስጥ አገልግሎት መስጫ ጽ/ቤቶችን በማቋቋም አገልግሎት መስጠት ይጀምራል።