የኢትዮጵያ ፖስታ ላለፉት 131 ዓመታት በኢትዮጵያ እና በመላው ዓለም ግንባር ቀደም የግንኙነት ምሰሶ በመሆን ሰዎችን ከሰዎች ተቋማትን ከተቋማት በማገናኘት ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ፖለቲካዊና ባህላዊ ትስስር እንዲጠነክርና የንግድ ልውውጥ እንዲያድግ የበኩሉን አስተዋፅዖ ሲያበረክት የቆየ አንጋፋ የህዝብ ተቋም ነው።
በቀድሞ ጊዜ ከነበረው የፖስታ ልውውጥ አሰራር አንስቶ እስከ አሁኑ ዘመናዊ የሎጂስቲክስና የዲጂታል ዘመን ከሁኔታዎችና ወቅታዊ ፍላጐቶች ጋር እራሱን በማስተዋወቅና በማዘመን እንዲሁም የአገልግሎት አድማሱንና ተደራሽነቱን በማስፋት ላለፉት አንድ መቶ ሠላሣ አንድ ዓመታት በትጋትና በአገልጋይነት መንፈስ ተጉዟል።
ዛሬም ይህን ትውልዶች የተቀባበሉትን አስደናቂ ምዕራፍ 131ኛ የምስረታ በዓል ስናከብር የዚህ ጉዞ አካል የሆኑትን ውድ ሰራተኞቻችንን፣ ውድ ደንበኞቻችንን እና አጋሮቻችንን በማመስገንና ላበረከቱት አስተዋፅዖ እውቅና በመስጠት ነው።
በቀጣይም አኩሪ የሕዝብ አገልጋይነት ታሪካችንን ሰንቀን ያሁኑንና ቀጣዩን ትውልድ ለማገልገል ይረዳን ዘንድ ቴክኖሎጂን በማቀፍ፣ አዳዲስ የአሰራር ስልቶችን በመንደፍና የደንበኞችን ፍላጎት ማዕከል በማድረግ ሁሌም ከትናንቱ በተሻለ ልናገለግልዎ ዝግጁ መሆናችንን በመግለጽ ነው።
መልካም 131ኛ ዓመት!