በኢትዮጵያ ፖስታ እና በእልባት ማኔጅመንት እና ቴክኖሎጂ ሶሉሽን መካከል በጋራ ለመስራት የሚያስችል ውል ተፈረመ፡፡
በተቋማቱ መካከል የተደረገው ስምምነት የኢትዮጵያ ፖስታ የአገልግሎት መስጫ ማዕከላትን ለማስፋፋት ያለመ መሆኑ ተጠቁሟል።
ስምምነቱን የኢትዮጵያ ፖስታን በመወከል ወ/ሮ ትዕግስት በቀለ ቺፍ ኮሜርሻል ኦፊሰር እና በእልባት ማኔጅመንት እና ቴክኖሎጂ ሶሉሽን በኩል ደግሞ ዋና ሥራ አስፈጻሚው አቶ ነፃነት ራያ ተፈራርመዋል፡፡
በተያያዘም በፊርማ ሥነስርዓቱ ላይ ወ/ሮ ትዕግስት በቀለ እንደገለጹት ይህ ስምምነት የኢትዮጵያ ፖስታ እየተገበረ ያለውን ስትራቴጂክ እቅድ ከማሳካት አንጻር የአገልግሎት ተደራሽነቱን በመጨምር እና የደንበኞችን እርካታ ከፍ በማድረግ የሚኖረው ሚና ጉልህ እንደሚሆን አብራርተዋል፡፡
የእልባት ማኔጅመንት እና ቴክኖሎጂ ሶሉሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ነፃነት ራያም በበኩላቸው በኢትዮጵያ አንጋፋ ከሆነው የኢትዮጵያ ፖስታ ጋር ለመሥራት ስምምነት ላይ በመድረሳቸው የተሰማቸውን ደስታ ገልጸው በድርጅታቸው ስር ባሉ በርካታ ኤጀንቶች አማካኝነት የኢትዮጵያ ፖስታን አገልግሎቶች በቅርቡ ለተገልጋዩ ህብረተሰብ ማድረስ እንደሚጀምሩ ገልጸዋል፡፡













