የኢትዮጵያ ፖስታ የሰራተኞችን ትጋት፣ ቁርጠኝነትና ስኬት ለማክበር እና ለማጠናከር ያዘጋጀው ዓመታዊ የሰራተኞች ቀን ዝግጅት በ ጥር 16 እና 17/2018 ዓ.ም በተለያዩ አበረታችና አዝናኝ መርሐ ግብሮች በደማቅ መንፈስ ተከናውኗል።
በመክፈቻው ስነ-ስርዓት ላይ የኢትዮጵያ ፖስታ ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ዳግማዊ ኃይልዬ ተገኝተው፣ ለላቀ አፈጻጸም ያሳዩ ሰራተኞች እንዲሁም በፖስታ ገበያ (Posta Gebeya) እና ቨርቹዋል ፖስታ ሳጥን አገልግሎቶች ዝግጅት እና ትግበራ ላይ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ላበረከቱ አመራሮችና ሰራተኞች የምስጋና እውቅና እና ምስክር ወረቀት ሰጥተዋል።
ዋና ስራ አስፈጻሚው በንግግራቸው በቀጣይ ተቋማዊ ግቦችን ለማሳካት ሁሉም ሰራተኛ በከፍተኛ መነሳሳትና ቁርጠኝነት መስራት እንዳለበትም አሳስበዋል። በዝግጅቱ ላይ ከሁሉም ዲስትሪክቶች በተወጣጡ ሰራተኞች መካከል የአንድነትና የቡድን መንፈስን የታየባቸው የእግር ኳስ ግጥሚያዎች ተካሂደዋል፡፡
በቀጣዩ ቀን በጉጉት ሲጠበቅ የነበረው በከፍተኛ አመራሮች እና በዲስትሪክት ዳይሬክተሮች መካከል የተካሄደው እና በአዝናኝነት የተሞላው የእግር ኳስ ግጥሚያ በመጨረሻ በከፍተኛ አመራሮች አሸናፊነት ተጠናቋል።
ከዚህ በተጨማሪ በሁለቱም ጾታ የዕለቱን ድባብ ከፍ ያደረጉ እና እድምተኞችን ያዝናኑ የእግር ኳስ ግጥሚያ፣ የገመድ ጉተታ፣ የማዳበሪያ ዝላይ እና እንቁላል በአፍ ይዞ መሮጥ ውድድሮች ተካሂደዋል:: በመዝጊያው እለት ለዘመናት ተቋሙን በታማኝነት ያገለገሉ እና በጡረታ ለሚለዩ አንጋፋ ሰራተኞችም የክብር አሸኛኘት ተደርጓል።















